Skip to content Skip to sidebar Skip to footer

የመካነ ሕይወት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ወርሃዊ የልምድ ልውውጥ ለወጣቶች እየሰጠች ትገኛለች

የመካነ ሕይወት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ወርሃዊ የልምድ ልውውጥ ለወጣቶች እየሰጠች ትገኛለች
ቦስተን የሚገኘው የመካነ ሕይወት ቅዱስ ሚካኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወጣቶች
በመንፈሳዊና እና በአለማዊ ህይወታቸው ያላቸውን እውቀት ለማጎልበት የሚያስችል የልምድ ልውውጥ
ከተወሰኑ ወራቶች በፊት የጀመረ ሲሆን በተለያዩ ደረጃ ላይ የሚገኙ የቤተ ክርስቲያኒቷን ምዕመናን በመጋበዝ
መርሃ ግብሩን እያቀረበ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል። ከጥቂት ወራት በፊት የተጀመረው ይህ ዝግጅት በየወሩ
እሁድ ከቅዳሴ በኋላ በቤተ ክርስቲያኑ የታችኛው ክፍል በመሰጠት ላይ እንደሚገኝ ተገልጿል።

ይህ መርሃ ግብር ስለ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መሰረታዊ እና ዝርዝር መረጃዎችን የሚያቀርብ ሲሆን ከዚህ
በተጨማሪ ተጋባዥ እንግዶቹ አንዳንድ ጊዜ በኮሌጅ ቆይታቸው ወቅት መንፈሳዊ ህይወታቸው ምን አይነት
መልክ እንደነበረው እና ያጋጠማቸውን ችግሮች ለታዳሚ ወጣቶቹ እንደሚገልጹ ለመረዳት ተችሏል ። እንግዶቹ
ለወጣቶቹ ካሉባቸው ሁኔታዎች አንጻር ያለፉባቸውን ሌሎች ጠቃሚ ልምዶች የሚያካፍሉ ሲሆን ወጣቶቹም
ተያያዥነት ያላቸውን ጥያቄዎች በመጠየቅ ተጨማሪ መረጃዎችን እንደሚያገኙ ተገልጿል። እስከ አሁን በነበረው
ዝግጅት ብዙ እንግዶች ተጋብዘው ለወጣቶቹ ገንቢ የሆኑ መልዕክቶችን ሲያስተላልፉ እንደቆዩ ለመረዳት ተችሏል።

በመካነ ህይወት የሰንበት ትምህርት ቤት ማለትም በአንቀጸ ተዋህዶ እየተዘጋጀ የሚቀርበው ይህ መርሃ ግብር ተጠናክሮ
እንዲቀጥል ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው የሚገልጹት ወላጆች ይህ መሰሉ የልምድ ልውውጥ ሰፋ ባለ መልኩ ተጠናክሮ
እንዲቀጥል ሃሳባቸውን ጨምረው ገልጸዋል።ይህንን ዝግጅት በቅርበት ከሚከታተሉ የሰንበት ትምህርት ቤቱ አባላት
ለመረዳት እንደተቻለው ይህ መርሃ ግብር ሁኔታዎች እስከፈቀዱ ድረስ እንደሚቀጥል ተሰፋቸውን ገልጸዋል።

የመካነ ሕይወት ቅዱስ ሚካኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህንን እና ሌሎች ትምህርታዊ
ዝግጅቶች በማዘጋጀት ልጆቿን በመንከባከብ በመንፈሳዊ እና በአለማዊ ህይወታቸው የተሳካ እንዲሆን እና
በማህበረሰቡ ውስጥ ጠቃሚ ዜጋ እንዲሆኑ የምታደርገው ይበል የሚያሰኝ ከፍተኛ እንቅስቃሴ ያላትን ጠንካራ
ቁርጠኝነት ያረጋግጣል።